Lamentations 3

א አሌፍ

የዚህ ምዕራፍ እያንዳንዱ አንጓ ተከታታይ ፊደላት ባሉት የዕብራይስጥ ሆህያት የሚጀምር ሲሆን፣ በእያንዳንዱ አንጓ ውስጥ ያሉት ጥቅሶች በአንድ ዐይነት ፊደል ይጀምራሉ።
1በቍጣው በትር፣
መከራ ያየ ሰው እኔ ነኝ።
2ከፊቱ አስወጣኝ፤
በብርሃን ሳይሆን በጨለማ እንድሄድ አደረገኝ።
3በርግጥ ቀኑን ሁሉ በመደጋገም፣
እጁን በላዬ ላይ መለሰ።
ב ቤት

4እርሱ ሥጋዬንና ቈዳዬን አስረጀ፤
ዐጥንቶቼንም ሰባበረ።
5በምሬትና በድካም፣
ቅጥር ሠራብኝ፤ ዙሪያዬንም ከበበኝ።
6ከሞቱ ብዙ ጊዜ እንደ ሆናቸው፣
በጨለማ እንድኖር አደረገኝ።
ג ጊሜል

7በቅጥር ውስጥ ዘጋብኝ፤ ስለዚህ ማምለጥ አልቻልሁም፤
የእስር ሰንሰለቴንም አከበደብኝ።
8ርዳታ ፈልጌ ብጣራና ብጮኽ እንኳ፣
ጸሎቴን መስማት አልፈለገም።
9መንገዴን በተጠረቡ ድንጋዮች ዘጋ፤
ጐዳናዬንም አጣመመ።
ד ዳሌት

10አሸምቆ እንደ ተኛ ድብ፣
እንደ አደባም አንበሳ፣
11ከመንገድ ጐትቶ አስወጣኝ፤ ቈራረጠኝም፤
ያለ ረዳትም ተወኝ።
12ቀስቱን ገተረ፤
ለፍላጻዎቹም ዒላማ አደረገኝ።
ה ሄ

13ፍላጻዎችን ከሰገባው አውጥቶ፣
ልቤን ወጋው።
14ለሕዝቤ ሁሉ ማላገጫ ሆንሁኝ፤
ቀኑን ሙሉ በመሣለቅ ያዜሙብኛል።
15መራራ ሥር አበላኝ፤
ሐሞትም አጠገበኝ።
ו ዋው

16ጥርሴን በድንጋይ ሰበረ፤
በትቢያ ውስጥ ረጋገጠኝ።
17ነፍሴ ሰላምን ዐጣች፤
ደስታ ምን እንደ ሆነ ረሳሁ።
18ስለዚህ፣ “ክብሬ፣
ከእግዚአብሔርም ተስፋ ያደረግሁት ሁሉ ሄዷል” አልሁ።
ז ዛይን

19የጭንቀቴንና የመንከራተቴን፣
ምሬትንና ሐሞትን ዐስባለሁ።
20ዘወትር አስበዋለሁ፤
ነፍሴም በውስጤ ተዋርዳለች።
21ሆኖም ይህን ዐስባለሁ፤
እንግዲያስ ተስፋ አለኝ፤
ח ኼት

22ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ታላቅ ፍቅር የተነሣ ነው፤
ርኅራኄው አያልቅምና።
23ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው፤
ታማኝነትህም ብዙ ነው።

24ራሴን እንዲህ አልሁት፤ “እግዚአብሔር ዕድል ፈንታዬ ነው፤
ስለዚህ ተስፋ አደርገዋለሁ።”
ט ቴት

25እርሱን ተስፋ ለሚያደርጉት፣
ለሚፈልገውም ሰው እግዚአብሔር መልካም ነው።
26ሰው የእግዚአብሔርን ማዳን፣
ዝም ብሎ ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው።
27ሰው በወጣትነቱ፣
ቀንበር ቢሸከም መልካም ነው።
י ዮድ

28ብቻውን ዝም ብሎ ይቀመጥ፤
እግዚአብሔር አሸክሞታልና።
29ፊቱን በዐቧራ ውስጥ ይቅበር፤
ተስፋ ሊኖር ይችላልና።
30ጕንጩን ለሚመታው ሰው ይስጥ፤
ውርደትንም ይጥገብ።
כ ካፍ

31ጌታ ሰውን፣
ለዘላለም አይጥልምና፤
32መከራን ቢያመጣ እንኳ ይራራል፤
ታላቅ ፍቅሩ አይለወጥምና።
33ሆን ብሎ ችግርን፣
ወይም መከራን በሰው ልጆች ላይ አያመጣምና።
ל ላሜድ

34የምድሪቱ እስረኞች ሁሉ፣
በእግር ሲረገጡ፣
35በልዑል ፊት፣
ሰው መብቱ ሲነፈገው፣
36ሰው ፍትሕ ሲጓደልበት፣
ጌታ እንዲህ ዐይነቱን ነገር አያይምን?
מ ሜም

37ጌታ ካላዘዘ በቀር፣
ተናግሮ መፈጸም የሚችል ማን ነው?
38ክፉም ሆነ መልካም ነገር፣
ከልዑል አፍ የሚወጣ አይደለምን?
39ታዲያ ሕያው ሰው በኀጢአቱ ሲቀጣ፣
ስለ ምን ያጕረመርማል?
נ ኑን

40መንገዳችንን እንመርምር፤ እንፈትን፤
ወደ እግዚአብሔርም እንመለስ።
41ልባችንን ከእጃችን ጋር በሰማይ ወዳለው ወደ አምላካችን
እናንሣ፤ እንዲህም እንበል፤
42“ዐምፀናል፤ ኀጢአትም ሠርተናል፤
አንተም ይቅር አላልኸንም።
ס ሳሜክ

43“ራስህን በቍጣ ከደንህ፤ አሳደድኸንም፤
ያለ ርኅራኄም ገደልኸን።
44ጸሎት እንዳያልፍ፣
ራስህን በደመና ሸፈንህ።
45በአሕዛብ መካከል፣
አተላና ጥራጊ አደረግኸን።
ע ዐዪን

46“ጠላቶቻችን ሁሉ፣
አፋቸውን በእኛ ላይ ከፈቱ።
47በጥፋትና በመፈራረስ፣
በችግርና በሽብር ተሠቃየን።”
48የእንባ ጐርፍ ከዐይኔ ፈሰሰ፤
ሕዝቤ ዐልቋልና።
פ ፌ

49ያለ ዕረፍት፣
ያለ ማቋረጥ ዐይኖቼ እንባ ያፈስሳሉ፤
50 እግዚአብሔር ከላይ፣
ከሰማይ እስኪያይ ድረስ።
51በከተማዬ ባሉት ሴቶች ሁሉ ላይ የደረሰውን ማየቴ፣
ነፍሴን አስጨነቃት።
צ ጻዲ

52ያለ ምክንያት ጠላቶቼ የሆኑ፣
እንደ ወፍ ዐደኑኝ።
53ሕይወቴን በጕድጓድ ውስጥ ሊያጠፉ ሞከሩ፣
ድንጋይም በላዬ አደረጉ።
54ውሃ ሞልቶ በዐናቴ ላይ ፈሰሰ፤
ጠፍቻለሁ ብዬ አሰብሁ።
ק ቆፍ

55በጥልቁ ጕድጓድ ውስጥ ሳለሁ፣
እግዚአብሔር ሆይ፤ የአንተን ስም ጠራሁ።
56ልመናዬን ሰምተሃል፤ “ርዳታም ፈልጌ ስጮኽ፣
ከመስማት ጆሮህን አትከልክል።”
57በጠራሁህ ጊዜ ቀረብኸኝ፣
እንዲሁም፣ “አትፍራ” አልኸኝ።
ר ሬሽ

58ጌታ ሆይ፤ ለእኔ ተሟገትኽልኝ፤
ሕይወቴንም ተቤዠህ።
59 እግዚአብሔር ሆይ፤ በእኔ ላይ የተደረገውን ግፍ አየህ፤
ፍርዴን ፍረድልኝ!
60በቀላቸውን ሁሉ፣
በእኔም ላይ ያሰቡትን ዐድማ አየህ።
ש ሲን እና ሺን

61 እግዚአብሔር ሆይ፤ ስድባቸውን ሁሉ፣
በእኔ ላይ ያሰቡትን ዐድማ ሁሉ ሰማህ፤
62ይህም ቀኑን ሙሉ በእኔ ላይ፣
ጠላቶቼ የሚያውጠነጥኑትና የሚያንሾካሹኩት ነው።
63ተመልከታቸው! ቆመውም ሆነ ተቀምጠው፣
በዘፈናቸው ይሣለቁብኛል።
ת ታው

64 እግዚአብሔር ሆይ፤ እጆቻቸው ላደረጉት፣
የሚገባውን መልሰህ ክፈላቸው።
65በልባቸው ላይ መጋረጃን ዘርጋ፤
ርግማንህም በላያቸው ይሁን!
66 ከእግዚአብሔር ሰማያት በታች፣
በቍጣህ አሳድዳቸው፤ አጥፋቸውም።
Copyright information for AmhNASV